በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 16

ኢዮብ ማን ነበር?

ኢዮብ ማን ነበር?

ዖጽ በሚባል አገር የሚኖር ይሖዋን የሚያመልክ አንድ ሰው ነበር። ይህ ሰው ኢዮብ ይባላል። ኢዮብ ብዙ ልጆች ያሉት ሀብታም ሰው ነበር። ደግ ስለነበር ድሆችን፣ ባሎቻቸው የሞቱባቸውን ሴቶች እንዲሁም ወላጅ የሌላቸውን ልጆች ይረዳ ነበር። ግን ኢዮብ ጥሩ ሰው ስለሆነ ብቻ ምንም ችግር አያጋጥመውም ማለት ነው?

ሰይጣን ዲያብሎስ ኢዮብን ያየው ነበር፤ ኢዮብ ግን ሰይጣን እያየው መሆኑን አያውቅም ነበር። ይሖዋ ሰይጣንን እንዲህ አለው፦ ‘አገልጋዬን ኢዮብን አየኸው? በምድር ላይ እንደ እሱ ያለ ሰው የለም። እኔ የምለውን ይሰማል፤ እንዲሁም ትክክል የሆነውን ነገር ያደርጋል።’ ሰይጣንም እንዲህ ብሎ መለሰ፦ ‘ታዲያ ቢታዘዝህ ምን ይገርማል? መጥፎ ነገር እንዳይደርስበት ትጠብቀዋለህ፤ የሚያስፈልገውን ሁሉ ትሰጠዋለህ። መሬትና እንስሳት ሰጥተኸዋል። እስቲ የእሱ የሆነውን ነገር ሁሉ ውሰድበት፤ አንተን ማምለኩን ይተዋል።’ ከዚያም ይሖዋ ‘ከፈለክ ኢዮብን ልትፈትነው ትችላለህ። እንድትገድለው ግን አልፈቅድልህም’ አለው። ይሖዋ፣ ሰይጣን ኢዮብን እንዲፈትነው የፈቀደለት ለምንድን ነው? ኢዮብ ፈተና ቢደርስበትም ለእሱ ታማኝ እንደሚሆን እርግጠኛ ስለነበረ ነው።

ሰይጣን ኢዮብን ለመፈተን የተለያዩ አደጋዎች አደረሰበት። በመጀመሪያ፣ ሳባውያን የሚባሉ ሰዎችን ልኮ የኢዮብን ከብቶችና አህዮች እንዲወስዱበት አደረገ። ቀጥሎ ደግሞ የኢዮብ በጎች በእሳት ተቃጥለው ሞቱ። ከለዳውያን የሚባሉ ሌሎች ሰዎች ደግሞ ድንገት መጥተው ግመሎቹን ወሰዱበት። እንስሳቱን እየጠበቁ የነበሩት አገልጋዮችም ተገደሉ። ቀጥሎ የደረሰው አደጋ ደግሞ ከዚህ ሁሉ የባሰ ነበር። የኢዮብ ልጆች በሙሉ አንድ ላይ ተሰብስበው እየበሉና እየጠጡ ሳሉ የነበሩበት ቤት እላያቸው ላይ ፈርሶ ሞቱ። ኢዮብ በጣም አዘነ፤ ይሖዋን ማምለኩን ግን አላቆመም።

ሰይጣን ኢዮብን የበለጠ ማሠቃየት ፈለገ፤ ስለዚህ ሰውነቱ በሙሉ እንዲቆስል አደረገ። ኢዮብ ቁስሉ በጣም ያሠቃየው ነበር። ይህ ሁሉ ችግር የደረሰበት ለምን እንደሆነ አላወቀም። ሆኖም ኢዮብ ይሖዋን ማምለኩን አልተወም። አምላክ ይህን ሲያይ በጣም ተደሰተ።

ከዚያም ሰይጣን ኢዮብን ለመፈተን ሦስት ሰዎችን ላከ። ሰዎቹ ኢዮብን እንዲህ አሉት፦ ‘ይህ ሁሉ የደረሰብህ የሠራኸውን ኃጢአት ለመደበቅ ሞክረህ መሆን አለበት። አምላክ እየቀጣህ ነው።’ ኢዮብም ‘እኔ ምንም የሠራሁት ጥፋት የለም’ ሲል መለሰ። በኋላ ግን ይህን ሁሉ ችግር ያመጣበት ይሖዋ እንደሆነ አድርጎ ስላሰበ አምላክ መጥፎ ነገር እንደፈጸመበት ተናገረ።

ይህን ሲነጋገሩ ኤሊሁ የሚባል አንድ ወጣት ዝም ብሎ እያዳመጠ ነበር። በኋላም እንዲህ በማለት ተናገረ፦ ‘ሁላችሁም የተናገራችሁት ነገር ስህተት ነው። እኛ ስለ ይሖዋ የማናውቀው ብዙ ነገር አለ። እሱ መጥፎ ነገር ሊያደርግ አይችልም። ሁሉንም ነገር ያያል፤ እንዲሁም ችግር የደረሰባቸውን ሰዎች ይረዳል።’

ከዚያም ይሖዋ ኢዮብን አነጋገረው። እንዲህ አለው፦ ‘እኔ ሰማይንና ምድርን ስሠራ አንተ የት ነበርክ? መጥፎ ነገር እንደፈጸምኩብህ አድርገህ የምትናገረው ለምንድን ነው? ይህ ሁሉ ነገር የሆነው ለምን እንደሆነ ሳታውቅ እንዴት ዝም ብለህ ትናገራለህ?’ ኢዮብ ስህተት እንደሠራ በማመን እንዲህ አለ፦ ‘ተሳስቻለሁ። ስለ አንተ ሰምቼ ነበር፤ አሁን ግን በደንብ አወቅኩህ። አንተ ምንም የሚያቅትህ ነገር የለም። እባክህ ይቅርታ አድርግልኝ።’

ፈተናው ሲያበቃ ይሖዋ ኢዮብን ከበሽታው አዳነው፤ እንዲሁም ከበፊቱ የበለጠ ብዙ ሀብት ሰጠው። ከዚያ በኋላ ኢዮብ ደስተኛ ሆኖ ብዙ ዓመት ኖረ። ኢዮብ ከባድ ፈተና በደረሰበት ወቅትም እንኳ ታዛዥ ስለነበር ይሖዋ ባርኮታል። አንተስ ምንም ነገር ቢያጋጥምህ እንደ ኢዮብ ይሖዋን ማምለክህን ትቀጥላለህ?

“ስለ ኢዮብ ጽናት ሰምታችኋል፤ በውጤቱም ይሖዋ ያደረገለትን አይታችኋል።”—ያዕቆብ 5:11