በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 4

ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው?

ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው?

1. ኢየሱስ ወደ ሕልውና የመጣው እንዴት ነው?

ኢየሱስ በቀላሉ የሚቀረብ የሆነው ምን ዓይነት ባሕርያት ስለነበሩት ነው?​—ማቴዎስ 11:29፤ ማርቆስ 10:13-16

ከሰው ልጆች በተለየ መልኩ ኢየሱስ፣ ሰው ሆኖ በምድር ላይ ከመወለዱ በፊት በሰማይ መንፈሳዊ አካል ሆኖ ይኖር ነበር። (ዮሐንስ 8:23) ኢየሱስ የአምላክ የመጀመሪያ ፍጥረት ሲሆን ሌሎች ፍጥረታት በሙሉ በተፈጠሩበት ጊዜ በሥራው ተባብሯል። በይሖዋ በቀጥታ የተፈጠረው እሱ ብቻ በመሆኑ የአምላክ “አንድያ ልጅ” ተብሎ መጠራቱ የተገባ ነው። (ዮሐንስ 1:14) ኢየሱስ የአምላክ ቃል አቀባይ ሆኖ ስላገለገለ “ቃል” ተብሎም ተጠርቷል።​—ምሳሌ 8:22, 23, 30ን እና ቆላስይስ 1:15, 16ን አንብብ።

2. ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው ለምንድን ነው?

አምላክ በሰማይ የሚኖረውን የልጁን ሕይወት ማርያም ወደተባለች አንዲት ድንግል አይሁዳዊት ማህፀን በማዛወር ወደ ምድር ላከው። በመሆኑም ኢየሱስ ሰብዓዊ አባት አልነበረውም። (ሉቃስ 1:30-35) ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው (1) ስለ አምላክ እውነቱን ለማስተማር (2) በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ብንሆንም እንኳ የአምላክን ፈቃድ እንዴት ማድረግ እንደምንችል ምሳሌ ለመተው እና (3) ፍጹም ሕይወቱን “ቤዛ” አድርጎ ለመስጠት ነው።​—ማቴዎስ 20:28ን አንብብ።

3. ቤዛ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

ቤዛ፣ ሕይወቱ አደጋ ላይ የወደቀን ሰው ነፃ ለማውጣት የሚከፈል ዋጋ ነው። (ዘፀአት 21:29, 30) አምላክ የሰው ልጆችን ሲፈጥር እንዲያረጁና እንዲሞቱ ዓላማው አልነበረም። ይህን እንዴት እናውቃለን? አምላክ ለመጀመሪያው ሰው ለአዳም መጽሐፍ ቅዱስ “ኃጢአት” ብሎ የሚጠራውን ነገር ከፈጸመ እንደሚሞት ነግሮት ነበር። አዳም ኃጢአት ባይሠራ ኖሮ ፈጽሞ አይሞትም ነበር። (ዘፍጥረት 2:16, 17፤ 5:5) መጽሐፍ ቅዱስ፣ ሞት ወደ ዓለም ‘የገባው’ በአዳም ምክንያት እንደሆነ ይናገራል። በዚህ መንገድ አዳም ኃጢአትንና የኃጢአት ደሞዝ የሆነውን ሞትን ለዘሮቹ በሙሉ አስተላለፈ። ከአዳም ከወረስነው የሞት ቅጣት ነፃ ለመውጣት ቤዛ ያስፈልገናል።​—ሮም 5:12ን እና 6:23ን አንብብ።

እኛን ከሞት ነፃ ለማውጣት ቤዛ ሊከፍልልን የሚችለው ማን ነው? ሁላችንም ኃጢአተኛ በመሆናችን ስንሞት የምንከፍለው የራሳችንን ኃጢአት ደሞዝ ብቻ ነው። በመሆኑም ፍጽምና የጎደለው ማንኛውም ሰው ለሌሎች ኃጢአት ቤዛ መክፈል አይችልም።​—መዝሙር 49:7-9ን አንብብ።

4. ኢየሱስ መሞት ያስፈለገው ለምንድን ነው?

ከሰው ልጆች በተለየ መልኩ ኢየሱስ ፍጹም ነበር። በመሆኑም ኢየሱስ ምንም ዓይነት ኃጢአት ስላልሠራ መሞት አያስፈልገውም ነበር። የሞተው በራሱ ኃጢአት ሳይሆን ለሌሎች ኃጢአት ሲል ነው። አምላክ፣ ልጁ እንዲሞትልን ወደ ምድር በመላክ ለሰው ዘር ያለውን ከፍተኛ ፍቅር ገልጿል። ኢየሱስም ቢሆን አባቱን በመታዘዝና ለእኛ ኃጢአት ሲል ሕይወቱን በመስጠት እንደሚወደን አሳይቷል።​—ዮሐንስ 3:16ን እና ሮም 5:18, 19ን አንብብ።

ኢየሱስ የሞተው ለምንድን ነው? የሚለውን ቪዲዮ ተመልከት

5. ኢየሱስ በአሁኑ ወቅት ምን እያደረገ ነው?

ኢየሱስ በምድር ሳለ የታመሙትን ፈውሷል፤ የሞቱትን አስነስቷል፤ እንዲሁም ሰዎችን ከሥቃያቸው ገላግሏቸዋል። ይህም ታዛዥ ለሆኑ የሰው ዘሮች በሙሉ ወደፊት ለሚያከናውነው ነገር ናሙና ነው። (ማቴዎስ 15:30, 31፤ ዮሐንስ 5:28) ኢየሱስ ሲሞት አምላክ እንደገና ሕያው እንዲሆን በማድረግ መንፈሳዊ ሕይወት ሰጥቶታል። (1 ጴጥሮስ 3:18) ከዚያም ኢየሱስ በምድር ሁሉ ላይ ንጉሥ ሆኖ ለመግዛት የሚያስፈልገውን ሥልጣን ይሖዋ እስኪሰጠው ድረስ በአምላክ ቀኝ ሆኖ ሲጠባበቅ ነበር። (ዕብራውያን 10:12, 13) በአሁኑ ጊዜ ኢየሱስ በሰማይ ንጉሥ ሆኖ እየገዛ ሲሆን በምድር ላይ የሚገኙት የእሱ ተከታዮች ደግሞ በዓለም ዙሪያ ይህን ምሥራች እያወጁ ነው።​—ዳንኤል 7:13, 14ን እና ማቴዎስ 24:14ን አንብብ።

በቅርቡ ኢየሱስ ንጉሣዊ ሥልጣኑን በመጠቀም መከራንም ሆነ ለመከራ መንስኤ የሆኑትን ሁሉ ጠራርጎ ያጠፋል። ኢየሱስን በመታዘዝ በእሱ ላይ እምነት እንዳላቸው በተግባር የሚያሳዩ በሙሉ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የመኖር ተስፋ ያገኛሉ።​—መዝሙር 37:9-11ን አንብብ።