በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

 ተጨማሪ ክፍል

በዓላትን ማክበር ይኖርብናል?

በዓላትን ማክበር ይኖርብናል?

በአሁኑ ጊዜ በብዙ የዓለም ክፍሎች የሚከበሩት ተወዳጅ የሆኑ ሃይማኖታዊና ሃይማኖታዊ ያልሆኑ በዓላት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ አይደሉም። ታዲያ እነዚህ በዓላት የመጡት ከየት ነው? ቤተ መጻሕፍት ሄደህ አንዳንድ የማመሳከሪያ መጻሕፍትን የመመልከት አጋጣሚ ካለህ በምትኖርበት አካባቢ ተወዳጅ የሆኑ በዓላትን አስመልክተው የሚሰጡትን ሐሳብ ስትመለከት በጣም ልትገረም ትችላለህ። እስቲ ጥቂት ምሳሌዎች ተመልከት።

 በዓለ ትንሣኤ። ዚ ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ “በአዲስ ኪዳን ውስጥ በዓለ ትንሣኤ እንደተከበረ የሚጠቁም ምንም ፍንጭ የለም” ሲል ይገልጻል። በዓለ ትንሣኤ መከበር የጀመረው እንዴት ነው? ይህ በዓል ከአረማውያን አምልኮ የመነጨ ነው። ምንም እንኳ ይህ በዓል የኢየሱስን ትንሣኤ ለማሰብ ተብሎ የሚከበር ቢሆንም ከዚህ በዓል ጋር ተያይዘው የሚፈጸሙት ልማዶች ክርስቲያናዊ አይደሉም።

የዘመን መለወጫ ክብረ በዓላት። የዘመን መለወጫ በዓል የሚከበርበት ቀንና ከዚህ በዓል ጋር ተያይዘው የሚፈጸሙት ልማዶች እንደየአገሩ ሁኔታ ይለያያሉ። ዘ ወርልድ ቡክ ኢንሳይክሎፒዲያ ስለዚህ በዓል አመጣጥ ሲገልጽ እንዲህ ይላል:- “በ46 ከክርስቶስ ልደት በኋላ የሮማው ገዥ ጁልየስ ቄሣር፣ ጃንዋሪ [ጥር] 1 የዘመን መለወጫ ቀን እንዲሆን ወሰነ። ሮማውያን ይህን ቀን የበሮች፣ የመዝጊያዎችና የመጀመሪያ ወይም የመነሻ አምላክ ለሆነው ለጄነስ መታሰቢያ አደረጉት። የጃንዋሪ ወር የተሰየመው አንደኛው ወደፊት ሌላኛው ደግሞ ወደኋላ የሚመለከቱ ሁለት ፊቶች ባሉት በጄነስ ስም ነው።” ስለዚህ የዘመን መለወጫ ክብረ በዓላት በአረማውያን ልማዶች ላይ የተመሠረቱ ናቸው።

ሌሎች ክብረ በዓላት። በዓለም ዙሪያ የሚከበሩትን በዓላት ሁሉ መጥቀስ አይቻልም። ይሁን እንጂ ሰዎችን ወይም ሰብዓዊ ድርጅቶችን የሚያወድሱ በዓላት በይሖዋ ፊት ተቀባይነት የላቸውም። (ኤርምያስ 17:5-7፤ የሐዋርያት ሥራ 10:25, 26) በተጨማሪም የሃይማኖታዊ በዓላት አመጣጥ አምላክ በዓላቱን ይቀበላቸዋል ወይስ አይቀበላቸውም በሚለው ጉዳይ ላይ ለውጥ እንደሚያመጣ አስታውስ። (ኢሳይያስ 52:11፤ ራእይ 18:4) በዚህ መጽሐፍ 16ኛ ምዕራፍ ላይ የተጠቀሱት የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች አምላክ ሃይማኖታዊ ባልሆኑ በዓላት ላይ መካፈልን በተመለከተ ምን አመለካከት እንዳለው ማወቅ እንድትችል ይረዱሃል።