ዘፍጥረት 27:1-46

  • ይስሐቅ ያዕቆብን ባረከው (1-29)

  • ኤሳው መባረክ ቢፈልግም በድርጊቱ አልተጸጸተም (30-40)

  • ኤሳው ያዕቆብን ጠላው (41-46)

27  ይስሐቅ ባረጀና ዓይኖቹ ደክመው ማየት በተሳናቸው ጊዜ ታላቁን ልጁን ኤሳውን ወደ እሱ ጠርቶ+ “ልጄ ሆይ!” አለው። እሱም “አቤት!” አለው።  ይስሐቅም እንዲህ አለው፦ “እንግዲህ አሁን አርጅቻለሁ። የምሞትበትንም ቀን አላውቅም።  ስለሆነም አሁን መሣሪያዎችህን፣ የቀስት ኮሮጆህንና ደጋንህን ይዘህ ወደ ዱር ሂድ፤ አድነህም አምጣልኝ።+  እኔ የምወደው ዓይነት ጣፋጭ ምግብ ሠርተህ አቅርብልኝ። ከመሞቴም በፊት እንድባርክህ* ልብላው።”  ይሁን እንጂ ይስሐቅ፣ ልጁን ኤሳውን ሲያነጋግረው ርብቃ ታዳምጥ ነበር። ኤሳው አደን አድኖ ለማምጣት ወደ ዱር ወጣ።+  ርብቃም ልጇን ያዕቆብን እንዲህ አለችው፦+ “አባትህ ወንድምህን ኤሳውን እንዲህ ሲለው ሰምቻለሁ፦  ‘እስቲ አደን አድነህ አምጣልኝና ጣፋጭ ምግብ ሥራልኝ። እኔም ሳልሞት በይሖዋ ፊት እንድባርክህ ልብላ።’+  እንግዲህ ልጄ፣ አሁን የምልህን በጥሞና አዳምጥ፤ የማዝህንም አድርግ።+  አባትህ የሚወደው ዓይነት ጣፋጭ ምግብ እንዳዘጋጅለት እባክህ ወደ መንጋው ሂድና ፍርጥም ያሉ ሁለት የፍየል ጠቦቶች አምጣልኝ። 10  ከዚያም ከመሞቱ በፊት እንዲባርክህ ምግቡን ለአባትህ ታቀርብለትና ይበላል።” 11  ያዕቆብ እናቱን ርብቃን እንዲህ አላት፦ “ወንድሜ ኤሳው ሰውነቱ ፀጉራም ነው፤+ የእኔ ሰውነት ግን ለስላሳ ነው። 12  አባቴ ቢዳብሰኝስ?+ በእሱ ላይ እያሾፍኩበት ያለሁ ሊመስል ይችላል፤ ይህ ከሆነ ደግሞ በረከት ሳይሆን እርግማን አተርፋለሁ።” 13  በዚህ ጊዜ እናቱ “ልጄ፣ ለአንተ የታሰበው እርግማን ለእኔ ይሁን። ብቻ እኔ የምልህን አድርግ፤ ሄደህ ጠቦቶቹን አምጣልኝ” አለችው።+ 14  ስለዚህ ሄዶ ጠቦቶቹን አመጣ፤ ለእናቱም ሰጣት፤ እናቱም አባቱ የሚወደው ዓይነት ጣፋጭ ምግብ ሠራች። 15  ከዚያም ርብቃ ቤት ውስጥ ያስቀመጠችውን የታላቁን ልጇን የኤሳውን ምርጥ ልብስ ወስዳ ታናሹን ልጇን ያዕቆብን አለበሰችው።+ 16  በተጨማሪም የፍየል ጠቦቶቹን ቆዳ በእጆቹና ፀጉር በሌለው የአንገቱ ክፍል ላይ አደረገች።+ 17  ከዚያም የሠራችውን ጣፋጭ ምግብና ዳቦ ለልጇ ለያዕቆብ ሰጠችው።+ 18  እሱም ወደ አባቱ ገብቶ “አባቴ ሆይ!” አለው። እሱም መልሶ “አቤት! ለመሆኑ አንተ ማነህ ልጄ?” አለው። 19  ያዕቆብም አባቱን “እኔ የበኩር ልጅህ+ ኤሳው ነኝ። ልክ እንዳልከኝ አድርጌአለሁ። እንድትባርከኝ* እባክህ ቀና ብለህ ተቀመጥና አድኜ ካመጣሁት ብላ”+ አለው። 20  በዚህ ጊዜ ይስሐቅ ልጁን “እንዴት እንዲህ ቶሎ ቀናህ ልጄ?” አለው። እሱም መልሶ “አምላክህ ይሖዋ አምጥቶ እጄ ላይ ስለጣለልኝ ነው” አለው። 21  ከዚያም ይስሐቅ ያዕቆብን “ልጄ ሆይ፣ አንተ በእርግጥ ልጄ ኤሳው መሆንህን እንዳውቅ እስቲ ቀረብ በልና ልዳብስህ” አለው።+ 22  በመሆኑም ያዕቆብ ወደ አባቱ ወደ ይስሐቅ ቀረበ። እሱም ዳበሰውና “ድምፁ የያዕቆብ ድምፅ ነው፤ እጆቹ ግን የኤሳው እጆች ናቸው”+ አለ። 23  እጆቹ እንደ ወንድሙ እንደ ኤሳው እጆች ፀጉራም ስለነበሩ ማንነቱን አልለየውም። ስለዚህ ባረከው።+ 24  ከዚያም “በእርግጥ አንተ ልጄ ኤሳው ነህ?” ሲል ጠየቀው። እሱም “አዎ፣ ነኝ” አለው። 25  በመቀጠልም “በል እንግዲህ ልጄ፣ አድነህ ያመጣህልኝን እንድበላ አቅርብልኝ፤ ከዚያም እባርክሃለሁ”* አለው። እሱም አቀረበለትና በላ፤ እንዲሁም የወይን ጠጅ አመጣለትና ጠጣ። 26  ከዚያም አባቱ ይስሐቅ “ልጄ፣ እስቲ ቀረብ በልና ሳመኝ”+ አለው። 27  ስለዚህ ወደ እሱ ቀረበና ሳመው፤ ይስሐቅም የልጁን ልብስ ጠረን አሸተተ።+ ከዚያም ባረከው፤ እንዲህም አለው፦ “አቤት፣ የልጄ ጠረን ይሖዋ እንደባረከው መስክ መዓዛ ነው። 28  እውነተኛው አምላክ የሰማያትን ጠል፣+ የምድርን ለም አፈር+ እንዲሁም የተትረፈረፈ እህልና አዲስ የወይን ጠጅ ይስጥህ።+ 29  ሕዝቦች ያገልግሉህ፤ ብሔራትም ይስገዱልህ። የወንድሞችህ ጌታ ሁን፤ የእናትህም ወንዶች ልጆች ይስገዱልህ።+ የሚረግሙህ ሁሉ የተረገሙ ይሁኑ፤ የሚባርኩህም ሁሉ የተባረኩ ይሁኑ።”+ 30  ይስሐቅ ያዕቆብን ባርኮ እንዳበቃና ያዕቆብ ከአባቱ ከይስሐቅ ፊት እግሩ እንደወጣ ወንድሙ ኤሳው ከአደን ተመለሰ።+ 31  እሱም ደግሞ ጣፋጭ ምግብ አዘጋጅቶ ለአባቱ አቀረበለት፤ አባቱንም “እስቲ እንድትባርከኝ* አባቴ ይነሳና ልጁ አድኖ ካመጣለት ይብላ” አለው። 32  በዚህ ጊዜ አባቱ ይስሐቅ “አንተ ደግሞ ማን ነህ?” አለው። እሱም መልሶ “ልጅህ ነኛ! የበኩር ልጅህ ኤሳው”+ አለው። 33  ይስሐቅም በኃይል እየተንቀጠቀጠ “አደን አድኖ ያመጣልኝና ያቀረበልኝ ታዲያ ማን ነበር? እኔ እኮ አንተ ከመምጣትህ በፊት በላሁ፤ እንዲሁም ባረክሁት፤ ደግሞም የተባረከ ይሆናል!” አለው። 34  ኤሳው አባቱ የተናገረውን ሲሰማ ከፍ ባለ ድምፅ ምርር ብሎ እያለቀሰ አባቱን “አባቴ ባርከኝ፤ እኔንም ባርከኝ እንጂ!” አለው።+ 35  ይስሐቅ ግን “ወንድምህ ለአንተ የታሰበውን በረከት ለማግኘት አንድ ተንኮል ሠርቷል” አለው። 36  ኤሳውም እንዲህ አለ፦ “ስሙ ያዕቆብ* የተባለው መቼ ያለምክንያት ሆነ! የኔ የሆነውን ሲወስድብኝ ይህ ሁለተኛ ጊዜው ነው።+ የብኩርና መብቴን መውሰዱ+ ሳያንሰው አሁን ደግሞ በረከቴን ቀማኝ!”+ ከዚያም “ለእኔ ምንም በረከት አላስቀረህልኝም?” አለው። 37  ይስሐቅ ግን ኤሳውን እንዲህ አለው፦ “በአንተ ላይ ጌታ አድርጌ ሾሜዋለሁ፤+ እንዲሁም ወንድሞቹን ሁሉ አገልጋዮቹ እንዲሆኑ ሰጥቼዋለሁ። እህልና አዲስ የወይን ጠጅ እንዲበዛለት ባርኬዋለሁ፤+ ታዲያ ለአንተ ላደርግልህ የምችለው ምን የቀረ ነገር አለ ልጄ?” 38  ኤሳውም አባቱን “አባቴ ሆይ፣ ለእኔ የምትሆን አንዲት በረከት እንኳ የለችህም? አባቴ ባርከኝ። እኔንም ባርከኝ እንጂ!” አለው። ኤሳውም ከፍ ባለ ድምፅ ምርር ብሎ አለቀሰ።+ 39  ስለዚህ አባቱ ይስሐቅ እንዲህ አለው፦ “እንግዲህ መኖሪያህ ለም ከሆነው የምድር አፈር እንዲሁም በላይ ካሉት ሰማያት ጠል የራቀ ይሆናል።+ 40  በሰይፍህ ትኖራለህ፤+ ወንድምህንም ታገለግላለህ።+ ይሁንና እየተቅበጠበጥክ ባስቸገርክ ጊዜ ቀንበሩን ከጫንቃህ ላይ ሰብረህ ትጥላለህ።”+ 41  ይሁን እንጂ ኤሳው አባቱ ያዕቆብን ስለባረከው ለያዕቆብ ከፍተኛ ጥላቻ አደረበት።+ ኤሳውም በልቡ “ለአባቴ ሐዘን የምንቀመጥበት ቀን ሩቅ አይደለም።+ ከዚያ በኋላ ወንድሜን ያዕቆብን እገድለዋለሁ” ይል ነበር። 42  ርብቃ ታላቁ ልጇ ኤሳው ያለው ነገር ሲነገራት ወዲያውኑ ለታናሹ ልጇ ለያዕቆብ እንዲህ የሚል መልእክት ላከችበት፦ “ወንድምህ ኤሳው አንተን በመግደል ሊበቀልህ እያሰበ ነው።* 43  እንግዲህ ልጄ እኔ የምልህን አድርግ። ተነስተህ በካራን ወደሚገኘው ወደ ወንድሜ ወደ ላባ ሽሽ።+ 44  የወንድምህ ቁጣ እስኪበርድ ድረስ ለተወሰነ ጊዜ እሱ ጋ ተቀመጥ፤ 45  ወንድምህ ንዴቱ እስኪበርድለትና ያደረግክበትን እስኪረሳ ድረስ እዚያ ቆይ። እኔም እልክብህና አስጠራሃለሁ። ሁለታችሁንም በአንድ ቀን ለምን ልጣ?” 46  ከዚያ በኋላ ርብቃ ይስሐቅን እንዲህ ትለው ጀመር፦ “በሄት ሴቶች ልጆች የተነሳ ሕይወቴን ጠልቻለሁ።+ ያዕቆብም በዚህ አገር የሚገኙትን እንደነዚህ ያሉትን የሄት ሴቶች ልጆች የሚያገባ ከሆነ በሕይወት መኖር ለእኔ ምን ያደርግልኛል?”+

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ነፍሴ እንድትባርክህ።”
ወይም “ነፍስህ እንድትባርከኝ።”
ወይም “ነፍሴ ትባርክሃለች።”
ወይም “ነፍስህ እንድትባርከኝ።”
“ተረከዝ የሚይዝ፤ የሚተካ” የሚል ትርጉም አለው።
ወይም “አንተን እንደሚገድልህ በማሰብ ራሱን እያጽናና ነው።”