ለተሰሎንቄ ሰዎች የተጻፈ ሁለተኛው ደብዳቤ 1:1-12

  • ሰላምታ (1, 2)

  • የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች እምነት እያደገ ሄደ (3-5)

  • በማይታዘዙት ላይ የሚወሰድ የበቀል እርምጃ (6-10)

  • ለጉባኤው የቀረበ ጸሎት (11, 12)

1  አባታችን ከሆነው አምላክና ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር አንድነት ላለው የተሰሎንቄ ሰዎች ጉባኤ፣ ከጳውሎስ፣ ከስልዋኖስና* ከጢሞቴዎስ+ የተላከ ደብዳቤ፦  አባት ከሆነው አምላክና ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።  ወንድሞች፣ ስለ እናንተ አምላክን ሁልጊዜ ለማመስገን እንገፋፋለን። እምነታችሁ እጅግ እያደገ በመሄዱና ሁላችሁም እርስ በርስ የምታሳዩት ፍቅር እየጨመረ በመምጣቱ ይህን ማድረጋችን ተገቢ ነው።+  ስለዚህ እየደረሰባችሁ* ያለውን ስደትና መከራ ሁሉ ችላችሁ በመኖር+ ባሳያችሁት ጽናትና እምነት የተነሳ በአምላክ ጉባኤዎች መካከል እኛ ራሳችን ስለ እናንተ በኩራት እንናገራለን።+  ይህ ሁሉ አምላክ ትክክለኛ ፍርድ እንደፈረደ የሚያሳይ ማስረጃ ከመሆኑም በተጨማሪ መከራ እየተቀበላችሁለት ላለው የአምላክ መንግሥት ብቁ ሆናችሁ እንድትቆጠሩ የሚያደርግ ነው።+  ከዚህ አንጻር አምላክ መከራን ለሚያመጡባችሁ በአጸፋው መከራን መክፈሉ የጽድቅ እርምጃ ነው።+  መከራን የምትቀበሉት እናንተ ግን ጌታ ኢየሱስ ከኃያላን መላእክቱ ጋር+ ከሰማይ በሚገለጥበት ጊዜ+ ከእኛ ጋር እረፍት ይሰጣችኋል፤  የሚገለጠውም በሚንበለበል እሳት ነው፤ በዚያን ጊዜ አምላክን በማያውቁትና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ለሚገልጸው ምሥራች በማይታዘዙት ላይ የበቀል እርምጃ ይወስዳል።+  እነዚህ ሰዎች ዘላለማዊ ጥፋት ተፈርዶባቸው ከጌታ ፊት ይወገዳሉ፤+ ክብራማ ኃይሉንም አያዩም፤ 10  በዚያን ጊዜ ከቅዱሳኑ ጋር ሊከበር ይመጣል፤ በእሱ የሚያምኑም ሁሉ በአድናቆት ያዩታል፤ እናንተም የሰጠናችሁን ምሥክርነት በእምነት ስለተቀበላችሁ ከእነሱ መካከል ትቆጠራላችሁ። 11  በዚህ ምክንያት አምላካችን ለጥሪው+ ብቁዎች አድርጎ እንዲቆጥራችሁ እንዲሁም የወደደውን መልካም ነገር ሁሉና በእምነት ተገፋፍታችሁ የምታከናውኑትን ሥራ በኃይሉ አማካኝነት ሙሉ በሙሉ እንዲፈጽም ስለ እናንተ ሁልጊዜ እንጸልያለን። 12  ይህም በአምላካችንና በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ መሠረት የጌታችን የኢየሱስ ስም በእናንተ እንዲከበርና እናንተም ከእሱ ጋር ባላችሁ አንድነት እንድትከበሩ ነው።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ሲላስ ተብሎም ይጠራል።
ወይም “በጽናት እያሳለፋችሁት።”