በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

ከዓለም አካባቢ

▪ ባለፉት ስድስት ዓመታት ውስጥ “በዩናይትድ ስቴትስ ወደ 100,000 የሚጠጉ ሰዎች . . . ተገድለዋል።”—ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ፣ ዩናይትድ ስቴትስ

▪ ማኅበራዊ አገልግሎት የሚሰጥ አንድ ድረ ገጽ 29,000 ደንበኞቹ ወሲብ ነክ ወንጀል ፈጽመው ስለተፈረደባቸው የግል ማኅደራቸውን (profile) ሰርዞባቸዋል። “ወሲብ ነክ ወንጀል ፈጻሚዎቹ [በድረ ገጹ] ላይ የሚፈጥሩት የግል ማኅደር ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በማሻቀቡ አፋጣኝ እርምጃ እንዲወሰድ ግድ ብሏል” በማለት ሪቻርድ ብሉሜንታል የተባሉ የከነቲከት ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ተናግረዋል።—ሮይተር የዜና አገልግሎት፣ ዩናይትድ ስቴትስ

▪ ቻይና ከፍተኛ የሆነ የስም እጥረት አጋጥሟታል። . . . በ2006 የተደረገ አንድ ጥናት እንዳመለከተው ከ1.4 ቢሊዮን ቻይናውያን መካከል . . . 85 በመቶ የሚሆኑት የሚጠሩበት የቤተሰብ ስም ከ100 አይበልጥም።—ቻይና ዴይሊ፣ ቻይና

▪ “ሞተር ብስክሌት የሚያሽከረክሩ ሰዎች” በእያንዳንዱ ኪሎ ሜትር ርቀት በትራፊክ አደጋ የመሞታቸው አጋጣሚ ከመኪና አሽከርካሪዎች “32 በመቶ ከፍ ያለ ነው።”—ዩሲ በርክሌይ ዌልነስ ሌተር፣ ዩናይትድ ስቴትስ

ቱርክ ለይሖዋ ምሥክሮች እውቅና ሰጠች

ሐምሌ 31, 2007 በቱርክ የሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮች ሕጋዊ እውቅና አግኝተው መመዝገባቸውን በይፋ የሚያሳውቅ ደብዳቤ ደረሳቸው። እውቅና ማግኘታቸው ንብረት ለመግዛትና በባለቤትነት ለማስተዳደር፣ የመሰብሰቢያ ቦታ ለመከራየት፣ ከለጋሾች የሚያገኙትን ገንዘብ ለመቀበልና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በፍርድ ቤት ተከራክረው ሕጋዊ መብታቸውን ለማስከበር ያስችላቸዋል።

ኢንተርኔት “የኃፍረት ስሜትን ይቀንሳል”

በቃል ኪዳን የታሰሩ ሰዎች በትዳር ጓደኛቸው ላይ እንዲወሰልቱ ሁኔታዎችን የሚያመቻች አንድ የጀርመን ድረ ገጽ በሰጠው መግለጫ ላይ፣ 310,000 ተጠቃሚዎች እንዳሉትና በየቀኑም 1,000 ደንበኞች እንደሚመዘገቡ በጉራ ተናግሯል። ድርጅቱ ከትዳራቸው ውጪ ግንኙነት መጀመር የሚሹ ደንበኞቹን “ስም መቶ በመቶ በምስጢር” መያዝ በመቻሉ ኩራት እንደሚሰማው ገልጿል። ከድርጅቱ ዳይሬክተሮች አንዱ “የኢንተርኔት ተጠቃሚዎቹ ስም በምስጢር መያዙ የኃፍረት ስሜትን ይቀንሳል” እንዲሁም “ግልጽ ውይይት በማድረግ ልብ ለልብ ለመግባባት ሁኔታውን ቀላል” ያደርጋል በማለት ተናግረዋል። አንድ ሌላ ዳይሬክተር ደግሞ ኢንተርኔት በጋብቻ ላይ የመወስለቱን ተግባር ይበልጥ ተወዳጅ እንደሚያደርገው ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።

ችግር ፈጣሪ ቅሪተ አካሎች

የሳይንስ ሊቃውንት ብዙውን ጊዜ “በሰው የዝግመተ ለውጥ ሒደት ውስጥ” የመጨረሻዎቹ “ደረጃዎች” ሆሞ ሃቢሊስ፣ ሆሞ ኢሬክተስና ሆሞ ሳፒየንስ ወይም ዘመናዊው ሰው እንደሆኑ ይናገራሉ። ይሁን እንጂ፣ የሰው ቅድመ አያቶች እንደሆኑ ከሚነገርላቸው ከሆሞ ሃቢሊስ እና ከሆሞ ኢሬክተስ የሚፈረጁ ሁለት ቅሪተ አካሎች ኬንያ ውስጥ በጥቂት እርምጃዎች ርቀት መገኘታቸው አንዳንድ ሳይንቲስቶች ሁለቱም ዝርያዎች በአንድ ዘመን ኖረዋል የሚል መደምደሚያ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል። ይህን ዘገባ ካወጡት የሳይንስ ሊቃውንት መካከል ሚቭ ሊኬይ የተባሉት ሴት “[ሁለቱም] በአንድ ዘመን መኖራቸው ሆሞ ኢሬክተስ ከሆሞ ሃቢሊስ ተሻሽሎ መጥቷል የሚለውን እምነት ውድቅ ያደርገዋል” ብለዋል።

የአየሩ ጠባይ በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ይከፋል?

ብዙ ጀርመናውያን የአየሩ ጠባይ ይበልጥ መጥፎ የሚሆነው ከሥራ ቀኖች ይልቅ ቅዳሜና እሁድ ነው የሚል ጥርጣሬ አላቸው። ከአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የተሰባሰበው የ15 ዓመታት የአየር ሁኔታ መረጃ ይህ ጥርጣሬያቸው እውነት መሆኑን እንደሚያሳይ ዴር ሽፒገል ዘግቧል። ከቀኖች ሁሉ በጣም ሞቃት የሆነው ረቡዕ ሲሆን በጣም ቀዝቃዛው ደግሞ ቅዳሜ ነው። ዘወትር ቅዳሜ 15 በመቶ የሚያህል ተጨማሪ ዝናብ የሚጥል ሲሆን መጠኑም ዝናብ አልባ በሆኑት ሰኞ ቀኖች ከሚዘንበው በ10 በመቶ ይበልጣል። ማክሰኞ ከቅዳሜ ጋር ሲነጻጸር በአማካይ ከ15 ደቂቃ በላይ ፀሐይ ያገኛል። ተመራማሪዎች እንደሚናገሩት ከሆነ በሳምንቱ መሃል ወደ ከባቢ አየር የሚገባው ጭስ ቅዳሜና እሁድ መጠኑ ከፍተኛ ይሆናል፤ ይህ ጭስ የፀሐይ ብርሃንን መልሶ ስለሚያንጸባርቅና ለጤዛ መፈጠር አመቺ ስለሚሆን ደመና በቀላሉ ይፈጠራል።