በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሽፋኑ ርዕሰ ጉዳይ | አምላክን መውደድ ከባድ እንዲሆን ያደረጉ ውሸቶች

እውነት ነፃ ያወጣችኋል

እውነት ነፃ ያወጣችኋል

አንድ ቀን፣ ኢየሱስ በኢየሩሳሌም እየሰበከ ነበር፤ በወቅቱ ስለ አባቱ ስለ ይሖዋ ያስተማረ ከመሆኑም ሌላ በዘመኑ የነበሩትን የሐሰት ሃይማኖት መሪዎች አጋልጧል። (ዮሐንስ 8:12-30) ኢየሱስ በዚያ ቀን የተናገረው ነገር፣ በዛሬው ጊዜ ስለ አምላክ የሚነገሩ በብዙኃኑ ዘንድ ተቀባይነት ያገኙ እምነቶችን መመርመር የምንችለው እንዴት እንደሆነ ያስተምረናል። ኢየሱስ “በቃሌ ብትኖሩ በእርግጥ ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤ እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም ነፃ ያወጣችኋል” ብሏል።—ዮሐንስ 8:31, 32

“በቃሌ ብትኖሩ።” እዚህ ላይ ኢየሱስ፣ ሃይማኖታዊ ትምህርቶች “እውነት” መሆን አለመሆናቸውን መመዘን የምንችልበትን መሥፈርት ሰጥቶናል። ስለ አምላክ አንድ ትምህርት ስትሰማ፣ ‘ይህ ሐሳብ ኢየሱስ ከተናገራቸውና በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ከሚገኙ ሌሎች ሐሳቦች ጋር ይስማማል?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። ጳውሎስ ሲናገር ካዳመጡ በኋላ፣ “የሰሙት ነገር ትክክል መሆኑን ለማረጋገጥ በየዕለቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በሚገባ [የመረመሩትን]” ሰዎች ምሳሌ ተከተል።—የሐዋርያት ሥራ 17:11

በእነዚህ ተከታታይ ርዕሶች መጀመሪያ ላይ የተጠቀሱት ማርኮ፣ ሮዛ እና ሬይሞንድ ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት እምነቶቻቸውን በጥንቃቄ መርምረዋል። ታዲያ ምን ማወቅ ቻሉ?

ማርኮ፦ “እኔና ባለቤቴ ለምንጠይቃቸው ጥያቄዎች በሙሉ የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪያችን መልስ የሚሰጠን ከመጽሐፍ ቅዱስ ነበር። ለይሖዋ ያለን ፍቅር ማደግ የጀመረ ሲሆን በእኔና በባለቤቴ መካከል ያለው ዝምድናም እየጠነከረ ሄደ!”

ሮዛ፦ “ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ሳስብ ሰዎች፣ አምላክን በራሳቸው አመለካከት ለመግለጽ የሞከሩበት የፍልስፍና መጽሐፍ እንደሆነ ይሰማኝ ነበር። ቀስ በቀስ ግን ለጥያቄዎቼ ከመጽሐፍ ቅዱስ መልስ አገኘሁ። አሁን፣ ይሖዋ ለእኔ እውን ነው። እምነት ልጥልበት እንደምችል ይሰማኛል።”

ሬይሞንድ፦ “ስለ እሱ እንዳውቅ እንዲረዳኝ ወደ አምላክ ጸልዬ ነበር። ከዚያ ብዙም ሳይቆይ እኔና ባለቤቴ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ጀመርን። በመጨረሻ፣ ስለ ይሖዋ እውነቱን አወቅን! እሱ ምን ዓይነት አምላክ እንደሆነ ስናውቅ ደስታችን ወሰን አልነበረውም።”

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አምላክ የተነገሩ ውሸቶችን በማጋለጥ ብቻ ሳይወሰን ማራኪ ስለሆኑት የአምላክ ባሕርያት እውነቱን ይገልጽልናል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ያስጻፈው ቃሉ ሲሆን “አምላክ በደግነት የሰጠንን ነገሮች ማወቅ እንችል ዘንድ” ይረዳናል። (1 ቆሮንቶስ 2:12) ስለ አምላክ፣ ስለ ዓላማውና ስለ ወደፊቱ ሕይወታችን ብዙ ጊዜ ለሚነሱ አስፈላጊ የሆኑ ጥያቄዎች መጽሐፍ ቅዱስ ምን መልስ እንደሚሰጥ ለምን አትመረምርም? ከእነዚህ ጥያቄዎች ለአንዳንዶቹ የተሰጡትን መልሶች ለማግኘት www.ps8318.com/am በተሰኘው ድረ ገጻችን ላይ “የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች > መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው” የሚለውን ክፍል ተመልከት። በተጨማሪም መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ከፈለግህ በዚሁ ድረ ገጽ ላይ ያለውን ቅጽ መሙላት ወይም ከይሖዋ ምሥክሮች አንዱን ማነጋገር ትችላለህ። መጽሐፍ ቅዱስን ካጠናህ፣ አምላክን መውደድ ከምታስበው በላይ ቀላል እንደሚሆንልህ እርግጠኞች ነን።