በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ይቅር ማለት ሲባል ምን ማለት ነው?

ይቅር ማለት ሲባል ምን ማለት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 ይቅር ማለት ሲባል ለበደለን ሰው ይቅርታ ማድረግ ማለት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ይቅር ማለት” ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል ቀጥተኛ ትርጉም “መተው” የሚል ነው፤ ይህ አገላለጽ አንድ ሰው ያለበትን ዕዳ ሳያስከፍሉ መተውን ያመለክታል። ኢየሱስ “ዕዳ ያለባቸውን ሁሉ ይቅር ስለምንል ኃጢአታችንን ይቅር በለን” ብለው እንዲጸልዩ ተከታዮቹን ሲያስተምር ይህን ንጽጽር ተጠቅሟል። (ሉቃስ 11:4 የግርጌ ማስታወሻ) በተጨማሪም ምሕረት ስላላደረገው ባሪያ በተናገረው ምሳሌ ላይ ይቅር ማለትን ዕዳ ከመሰረዝ ጋር አመሳስሎታል።—ማቴዎስ 18:23-35

 አንድን ሰው ይቅር አልን የሚባለው ማንኛውንም ቅሬታ ካስወገድንና ለደረሰብን ጉዳት ወይም ኪሳራ ካሳ ካልጠየቅን ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ከልብ ይቅር ማለት የምንችለው ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ ፍቅር ካለን እንደሆነ ይናገራል፤ ምክንያቱም “ፍቅር የበደል መዝገብ የለውም።”—1 ቆሮንቶስ 13:4, 5

ይቅር ማለት የማያመለክታቸው ነገሮች

  •   የደረሰብንን በደል ችላ ማለት። መጥፎ ድርጊቶች ምንም ጉዳት እንደማያስከትሉ ወይም ተቀባይነት እንዳላቸው የሚናገሩ ሰዎችን መጽሐፍ ቅዱስ ያወግዛል።—ኢሳይያስ 5:20

  •   ምንም በደል እንዳልደረሰብን መቁጠር። አምላክ፣ ንጉሥ ዳዊት የፈጸማቸውን ከባድ ኃጢአቶች ይቅር ቢልም ድርጊቱ ካስከተለበት መዘዝ እንዲያመልጥ አላደረገውም። እንዲያውም ዳዊት የፈጸማቸውን ኃጢአቶች ዛሬም ድረስ የምናስታውሳቸው አምላክ ተመዝግበው እንዲቆዩ ስላደረገ ነው።—2 ሳሙኤል 12:9-13

  •   ሌሎች መጠቀሚያ ሲያደርጉን ዝም ብሎ መመልከት። ለምሳሌ ለአንድ ሰው ገንዘብ አበድረሃል እንበል። ሆኖም ግለሰቡ ገንዘቡን ስላባከነው መልሶ ሊከፍልህ አልቻለም። ባደረገው ነገር በጣም አዝኖ ይቅርታ ጠየቀህ። በዚህ ጊዜ ቂም ባለመያዝ፣ ጉዳዩን ደጋግሞ ባለማንሳት ምናልባትም ዕዳውን ሙሉ በሙሉ በመሰረዝ ይቅር ልትለው ትችላለህ። በሌላ በኩል ግን ዳግመኛ ለእሱ ገንዘብ ላለማበደር ልትወስን ትችላለህ።—መዝሙር 37:21፤ ምሳሌ 14:15፤ 22:3፤ ገላትያ 6:7

  •   ያለ በቂ ምክንያት ይቅር ማለት። አምላክ፣ ሆን ብለው ኃጢአት የሚሠሩ ሰዎችን እንዲሁም ስህተታቸውን ለማመን፣ አካሄዳቸውን ለመቀየርና የበደሏቸውን ሰዎች ይቅርታ ለመጠየቅ ፈቃደኛ ያልሆኑ ሰዎችን ይቅር አይልም። (ምሳሌ 28:13፤ የሐዋርያት ሥራ 26:20፤ ዕብራውያን 10:26) እንዲህ ያሉ ንስሐ የማይገቡ ሰዎች የአምላክ ጠላት ይሆናሉ፤ አምላክ ደግሞ እሱ ይቅር ያላላቸውን ሰዎች ይቅር እንድንል አይጠብቅብንም።—መዝሙር 139:21, 22

     አንድ ሰው ከባድ በደል ፈጽሞብህ ይቅርታ ለመጠየቅ ወይም ጥፋቱን ለማመን ፈቃደኛ ባይሆንስ? መጽሐፍ ቅዱስ “ከቁጣ ተቆጠብ፤ ንዴትንም ተው” የሚል ምክር ይሰጣል። (መዝሙር 37:8) ይቅርታ ባታደርግም እንኳ በንዴት እንዳትዋጥ ጥንቃቄ አድርግ። አምላክ ግለሰቡን ተጠያቂ እንደሚያደርገው እርግጠኛ ሁን። (ዕብራውያን 10:30, 31) በተጨማሪም አምላክ፣ በአሁኑ ጊዜ ሸክም የሆነብንን የስሜት ቁስል እንድንረሳው የሚያደርግበት ጊዜ እንደሚመጣ ማስታወስህ ሊያጽናናህ ይችላል።—ኢሳይያስ 65:17፤ ራእይ 21:4

  •   ለጥቃቅን ነገሮች “ይቅር” ማለት። አንዳንድ ጊዜ፣ እንደበደለን የተሰማንን ሰው ይቅር ስለ ማለት ከማሰብ ይልቅ መጀመሪያውኑም የሚያስከፋን በቂ ምክንያት እንዳልነበረን አምነን መቀበል ይኖርብናል። መጽሐፍ ቅዱስ “ቁጣ የሞኝ ሰው መለያ ስለሆነ ለቁጣ አትቸኩል” ይላል።—መክብብ 7:9 የግርጌ ማስታወሻ

ይቅር ማለት የምንችለው እንዴት ነው?

  1.   ይቅር ማለት ምን ትርጉም እንዳለው አስታውስ። ይቅርታ ማድረግ ሲባል በደልን ችላ ብሎ ማለፍ ወይም ጨርሶ እንዳልተፈጠረ መቁጠር ማለት ሳይሆን መተው ማለት ነው።

  2.   ይቅር ማለት ያለውን ጥቅም አስብ። አለመበሳጨትና ቂም አለመያዝ እንድትረጋጋ፣ ጤንነትህ እንዲሻሻልና ደስታህ እንዲጨምር ያደርጋል። (ምሳሌ 14:30፤ ማቴዎስ 5:9) ከሁሉም በላይ ደግሞ አምላክ ኃጢአታችንን ይቅር እንዲልልን ከፈለግን ሌሎችን ይቅር ማለት ይኖርብናል።—ማቴዎስ 6:14, 15

  3.   ራስህን በሌሎች ቦታ አስቀምጥ። ሁላችንም ፍጽምና ይጎድለናል። (ያዕቆብ 3:2) ሌሎች ይቅር እንዲሉን እንደምንፈልግ ሁሉ እኛም የሌሎችን ስህተት ይቅር ማለት ይኖርብናል።—ማቴዎስ 7:12

  4.   ምክንያታዊ ሁን። በትንሽ ነገር ከሰዎች ጋር ስንጋጭ “እርስ በርስ መቻቻላችሁን . . . ቀጥሉ” የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ተግባራዊ ማድረግ እንችላለን።—ቆላስይስ 3:13

  5.   አፋጣኝ እርምጃ ውሰድ። ያበሳጨህን ነገር እያሰብክ ከመብሰልሰል ይልቅ ወዲያውኑ ይቅር ለማለት ጥረት አድርግ።—ኤፌሶን 4:26, 27