በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ኑሯችንን ቀላል ለማድረግ ወሰንን

ኑሯችንን ቀላል ለማድረግ ወሰንን

 ማዲያን እና ማርሴላ፣ ሜደሊን በተባለች የኮሎምቢያ ከተማ ውስጥ የተደላደለ ሕይወት ይመሩ ነበር። ማዲያን ዳጎስ ያለ ደሞዝ የሚያስገኝ ሥራ ስለነበረው በሚያምር አፓርታማ ውስጥ ይኖሩ ነበር። ሆኖም የይሖዋ አምላክ አገልጋዮች እንደመሆናቸው መጠን በሕይወታቸው ውስጥ ቅድሚያ የሚሰጧቸውን ነገሮች እንዲገመግሙ የሚያነሳሳ ነገር አጋጠማቸው። እንዲህ ብለዋል፦ “በ2006 በተካሄደው ‘ጤናማ ዓይን ይኑራችሁ’ የተባለ ልዩ ስብሰባ ላይ ተካፍለን ነበር። በስብሰባው ላይ የቀረቡት ብዙዎቹ ንግግሮች፣ አምላክን በተሟላ መንገድ ለማገልገል ኑራችንን ቀላል በማድረግ ላይ ያተኮሩ ነበሩ። ከስብሰባው ወጥተን ወደ ቤት ስንመለስ፣ የእኛ አኗኗር ከዚህ በጣም የተለየ እንደሆነ ተገንዝበን ነበር። ያየነውን ሁሉ የመግዛት አባዜ ተጠናውቶን ነበር፤ በዚያ ላይ ደግሞ ብዙ ዕዳ ነበረብን።”

 ማዲያን እና ማርሴላ በስብሰባው ላይ ያገኙት ትምህርት እንደ ማንቂያ ደወል ስለሆነላቸው ኑራቸውን ቀላል ለማድረግ መጣር ጀመሩ። እንዲህ ብለዋል፦ “ወጪያችንን መቀነስ ጀመርን። አነስ ወዳለች አፓርታማ ተዛወርን፤ መኪናችንን ሸጠን ሞተር ብስክሌት ገዛን።” በተጨማሪም ዕቃ ለመግዛት እንዳይፈተኑ ሲሉ ወደ ገበያ አዳራሾች መሄዳቸውን አቆሙ። ለሰዎች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ በመናገር የበለጠ ጊዜ ያሳልፉ ጀመር። ከዚህም ሌላ ልዩ አቅኚዎች a ሆነው ይሖዋ አምላክን በቅንዓት ከሚያገለግሉ ወዳጆቻቸው ጋር የበለጠ ጊዜ ማሳለፍ ጀመሩ።

 ብዙም ሳይቆይ ማዲያን እና ማርሴላ በገጠራማ አካባቢ ወደሚገኝና እርዳታ ወደሚያስፈልገው አንድ ትንሽ ጉባኤ በመሄድ አገልግሎታቸውን ለማስፋት ወሰኑ። ማዲያን ወደዚያ ለመሄድ ሲል ሥራውን አቆመ። አለቃው የማዲያን ውሳኔ ጨርሶ ሊገባት አልቻለም። ስለዚህ ማዲያን ውሳኔውን ለማስረዳት “አንቺ ብዙ ገንዘብ ታገኛለሽ፤ ግን በሕይወትሽ ደስተኛ ነሽ?” ብሎ ጠየቃት። እሷም መፍትሔ ያላገኘችላቸው ብዙ ችግሮች ስላሉባት ደስተኛ እንዳልሆነች በሐቀኝነት ተናገረች። በዚህ ጊዜ ማዲያን እንዲህ አላት፦ “ዋናው ነገር የምናገኘው ገንዘብ መጠን አይደለም። እውነተኛ ደስታ የሚያስገኝልን ምን እንደሆነ ማወቅ ያስፈልገናል። እኔና ባለቤቴ ሰዎችን ስለ አምላክ ማስተማር ያስደስተናል፤ በመሆኑም በዚህ ሥራ የበለጠ ጊዜ በማሳለፍ የበለጠ ደስተኛ መሆን እንፈልጋለን።”

 ማዲያን እና ማርሴላ መንፈሳዊ ግቦችን በማስቀደማቸው እውነተኛ እርካታና ደስታ አግኝተዋል። ላለፉት 13 ዓመታት፣ በሰሜን ምዕራብ ኮሎምቢያ በሚገኙ ሰባኪዎች ይበልጥ የሚያስፈልጉባቸው ጉባኤዎች ውስጥ አገልግለዋል። አሁን ደግሞ ልዩ አቅኚዎች ሆነው በደስታ እያገለገሉ ነው።

a ልዩ አቅኚ የሚባሉት በተመደቡበት ቦታ ምሥራቹን በሙሉ ጊዜያቸው እንዲሰብኩ በአገራቸው ያለው የይሖዋ ምሥክሮች ቅርንጫፍ ቢሮ የሾማቸው ሰዎች ናቸው። ለኑሮ የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች ለማሟላት መጠነኛ የወጪ መሸፈኛ ይሰጣቸዋል።