በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

እውነትን ፍለጋ

እውነትን ፍለጋ

እውነትን ማወቅ የሕይወትና የሞት ጉዳይ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ‘በሽታ የሚተላለፈው እንዴት ነው?’ የሚለው ጥያቄ መልስ በሰው ልጆች ሕይወት ላይ ምን ለውጥ እንዳመጣ ለማሰብ ሞክር።

በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት የዚህ ጥያቄ መልስ አይታወቅም ነበር፤ በመሆኑም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች በወረርሽኝ ምክንያት ሕይወታቸው አልፏል። ከጊዜ በኋላ ግን የሳይንስ ሊቃውንት እውነቱን ደረሱበት። ተላላፊ በሽታዎች የሚመጡት እንደ ባክቴሪያ ወይም ቫይረስ ባሉ በሽታ አምጪ ተሕዋስያን ምክንያት እንደሆነ ተረጋገጠ። ከተላላፊ በሽታዎች ጋር በተያያዘ እውነቱ በመታወቁ በርካታ በሽታዎችን መከላከልና ማከም ተችሏል፤ በዚህም ምክንያት በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ረጅምና ጤናማ ሕይወት መምራት ችለዋል።

አሳሳቢ ስለሆኑ ሌሎች ጥያቄዎችስ ምን ማለት ይቻላል? ከዚህ በታች ስለቀረቡት ጥያቄዎች እውነቱን ማወቅህ በሕይወትህ ላይ ምን ለውጥ የሚያመጣ ይመስልሃል?

  • አምላክ ማን ነው?

  • ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው?

  • የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?

  • የወደፊቱ ጊዜ ምን ይዞ ይመጣል?

በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ በማወቃቸው ትርጉም ያለው ሕይወት መምራት ችለዋል። መልሶቹን ማወቅህ አንተንም ይጠቅምሃል።

እውነትን ማወቅ ይቻላል?

‘ስለ አንድ ነገር እውነቱን ማወቅ የሚቻለው እንዴት ነው?’ ብለህ ታስብ ይሆናል። ደግሞም ስለተለያዩ ነገሮች እውነቱን ማወቅ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል። ለምን?

ብዙ ሰዎች መንግሥታት፣ የንግድ ድርጅቶች እንዲሁም መገናኛ ብዙኃን እውነት እንደሚናገሩ አይሰማቸውም። የራሳቸውን አመለካከት፣ ከፊል እውነትነት ያለውን ሐሳብ አልፎ ተርፎም ዓይን ያወጣ ውሸትን እውነት አስመስለው የሚያቀርቡ ሰዎች በመበራከታቸው እውነታውን መለየት ከባድ እየሆነ መጥቷል። አለመተማመንና ውሸት በነገሠበት በዚህ ዓለም ውስጥ እውነታውን ተረድቶ ትክክለኛው መደምደሚያ ላይ መድረስ ይቅርና እውነቱን ከውሸቱ መለየት ራሱ አስቸጋሪ ነው።

እነዚህ ተፈታታኝ ነገሮች ቢኖሩም ለምናነሳቸው አንገብጋቢ ጥያቄዎች እውነተኛውን መልስ ማግኘት እንችላለን። እንዴት? በዕለት ተዕለት ሕይወታችን የምንጠቀምበትን ዘዴ ተግባራዊ በማድረግ ነው።

እውነትን ማግኘት የምትችለው እንዴት ነው?

በየቀኑ እውነትን እንፈልጋለን ሊባል ይችላል። ጄሲካን እንደ ምሳሌ እንውሰድ። ጄሲካ “ልጄ ከባድ የለውዝ አለርጂ አለባት። ለውዝ በትንሹ የገባበት ነገር እንኳ ብትበላ ሊገድላት ይችላል” ብላለች። በመሆኑም ጄሲካ ለልጇ ምግብ ስትገዛ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለባት። እንዲህ ብላለች፦ “የታሸገ ምግብ ስገዛ በመጀመሪያ ምግቡ ከምን ከምን እንደተሠራ ከሽፋኑ ላይ በጥንቃቄ አነብባለሁ። ከዚያም ተጨማሪ ምርምር አደርጋለሁ፤ እንዲያውም ትንሽ ለውዝ እንኳ በስህተት እንዳልተቀላቀለበት ለማረጋገጥ አምራቹን ድርጅት እጠይቃለሁ። በተጨማሪም ድርጅቱ ከምግብ ጤንነት ጋር በተያያዘ ምን ዓይነት ስም እንዳተረፈ ለማወቅ ከተአማኒ ምንጮች አጣራለሁ።”

በዕለት ተዕለት ሕይወትህ እውነትን ለማግኘት የምታደርገው ፍለጋ እንደ ጄሲካ የሕይወትና የሞት ጉዳይ ላይሆን ይችላል፤ ሆኖም ለጥያቄዎችህ መልስ ለማግኘት ልክ እንደ እሷ የሚከተለውን ዘዴ ትጠቀም ይሆናል፦

  • መረጃ ማግኘት።

  • ተጨማሪ ምርምር ማድረግ።

  • የመረጃ ምንጮችህ ተአማኒ መሆናቸውን ማረጋገጥ።

ይህ ዘዴ በሕይወታችን ላይ ትልቅ ለውጥ ለሚያመጡ ወሳኝ ጥያቄዎችም እውነተኛውን መልስ ለማግኘት ሊረዳን ይችላል። እንዴት?

እውነትን የያዘ ልዩ መጽሐፍ

ጄሲካ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለመመርመር የወሰደችው እርምጃ ስለ ልጇ የምግብ አለርጂ ምርምር ለማድረግ ከምትጠቀምበት ዘዴ ጋር ተመሳሳይ ነው። “መጽሐፍ ቅዱስን በጥንቃቄ ማንበቤና በትጋት ምርምር ማድረጌ እውነትን እንዳገኝ ረድቶኛል” ብላለች። ጄሲካን ጨምሮ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ለሚከተሉት ጥያቄዎች የሚሰጠውን መልስ ማወቅ ችለዋል፦

  • የሕይወት ዓላማ ምንድን ነው?

  • ስንሞት ምን እንሆናለን?

  • መከራ የሚደርስብን ለምንድን ነው?

  • አምላክ መከራን የሚያስወግደው እንዴት ነው?

  • አስደሳች የቤተሰብ ሕይወት መምራት የምንችለው እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብና www.ps8318.com ላይ ተጨማሪ ምርምር በማድረግ የእነዚህንና የሌሎችን ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ትችላለህ።