በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለታዳጊ ወጣቶች

ትልቅ ቦታ የማግኘት ምኞት እንዳያድርብህ ተጠንቀቅ!

ትልቅ ቦታ የማግኘት ምኞት እንዳያድርብህ ተጠንቀቅ!

መመሪያ፦ ይህን መልመጃ ጸጥታ በሰፈነበት ቦታ ሆነህ ሥራ። ጥቅሶቹን ስታነብ በቦታው እንዳለህ አድርገህ አስብ። ሁኔታውን በዓይነ ሕሊናህ ለመሳል እንዲሁም በታሪኩ ውስጥ የተጠቀሱት ሰዎች ሲነጋገሩ ድምፃቸውን ለመስማትና ስሜታቸውን ለመረዳት ሞክር። ታሪኩ ሕያው እንዲሆንልህ አድርግ።

ዋነኞቹ ባለታሪኮች፦ ዳዊት፣ አቤሴሎም እና ኢዮአብ

ታሪኩ በአጭሩ፦ አቤሴሎም የአባቱን ዙፋን ለመንጠቅ ሞከረ።

ሁኔታውን ለማስተዋል ሞክር።​—2 ሳሙኤል 14:25-33ን፣ 2 ሳሙ 15:1-17ን እና 2 ሳሙ 18:9-17, 30-33ን አንብብ።

አቤሴሎም ምን ዓይነት መልክና ቁመና የነበረው ይመስልሃል? (2 ሳሙኤል 14:25, 26ን በድጋሚ አንብብ።)

አቤሴሎም፣ ፍትሕ ለማግኘት ወደ ንጉሡ የሚመጡ ሰዎችን ልብ ለመማረክ በሚሞክርበት ጊዜ በምን መንገድ ይቀርባቸው እንዲሁም እንዴት ባለ የድምፅ ቃና ያነጋግራቸው የነበረ ይመስልሃል? (2 ሳሙኤል 15:2-6ን በድጋሚ አንብብ።)

በ⁠2 ሳሙኤል 14:28-30 ላይ ካለው ታሪክ በመነሳት አቤሴሎም ምን ዓይነት ሰው ይመስልሃል?

ጥልቅ ምርምር አድርግ።

አቤሴሎም፣ ንግሥናውን ለመጨበጥ ሁኔታዎችን ያመቻቸው እንዴት ነው? (ፍንጭ፦ 2 ሳሙኤል 13:28, 29ን አንብብ። አምኖን የዳዊት የመጀመሪያ ልጅ በመሆኑ ዙፋኑን የመውረስ መብት ያለው እሱ ነበር።)

አቤሴሎም ትልቅ ቦታ ለማግኘት የሚጓጓና የራሱን ክብር የሚፈልግ ሰው ቢሆንም ከተቀበረበት ሁኔታ ማየት እንደምንችለው ሰዎች ስለ እሱ ምን ዓይነት አመለካከት ነበራቸው? (2 ሳሙኤል 18:17ን በድጋሚ አንብብ።)

አቤሴሎም ትልቅ ቦታ የማግኘት ምኞት እንዲያድርበት አስተዋጽኦ ያደረገው ምን ይመስልሃል? (ዲዮጥራጢስን አስመልክቶ በ⁠3 ዮሐንስ 9, 10 ላይ ከሰፈረው ዘገባ ጋር አወዳድር።)

የአቤሴሎም ድርጊት በዳዊት ላይ ምን አስከትሏል? (ፍንጭ፦ ዳዊት፣ አቤሴሎም በእሱ ላይ ባመፀበት ወቅት የጻፈውን መዝሙር 3ን አንብብ።)

ከዚህ ታሪክ ያገኘኸውን ትምህርት ተግባራዊ አድርግ። ከዚህ በታች ስለሰፈሩት ሐሳቦች ምን ትምህርት እንዳገኘህ ጻፍ፦

ትልቅ ቦታ ለማግኘት መጓጓት ስላለው አደጋ

የአንድ ሰው ድርጊት በወላጆቹና በሌሎች ሰዎች ላይ ሊያስከትል ስለሚችለው ሥቃይ

ልትሠራበት የሚገባ ተጨማሪ ነገር፦

ትልቅ ቦታ ለማግኘት በመጓጓት ወጥመድ ልትያዝ የምትችለው እንዴት ነው?

ተገቢ ያልሆነ ኩራት እንዳያድርብህ ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?

ከዚህ ታሪክ ውስጥ ልብህን ይበልጥ የነካው ምንድን ነው? ለምንስ?

ተጨማሪ ሐሳብ፦ ይህ ታሪክ ከዚህ የተለየ ፍጻሜ ቢኖረው ምን ሊሆን እንደሚችል አስብ። አቤሴሎም ትልቅ ቦታ ለማግኘት ከመመኘት ይልቅ ትሑት ሰው ቢሆን ኖሮ ምን ዓይነት ሁኔታ ይኖር ነበር?—ምሳሌ 18:12