በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሽፋኑ ርዕሰ ጉዳይ | የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብን አስደሳች ማድረግ

መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ያለብኝ ለምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ያለብኝ ለምንድን ነው?

“መጽሐፍ ቅዱስ፣ ለመረዳት ከባድ የሆነ መጽሐፍ ይመስለኝ ነበር።”—ጁቪ

“በጣም አሰልቺ እንደሚሆን ተሰምቶኝ ነበር።”—ክዊኒ

“መጽሐፍ ቅዱስን ሳየው፣ መቼም ቢሆን አንብቤ ልጨርሰው እንደማልችል ስለተሰማኝ ተስፋ ቆረጥኩ።”—ኢዚክኤል

አንተስ ከላይ እንደተጠቀሱት ሰዎች ዓይነት ስሜት ተሰምቶህ ያውቃል? በዚህ የተነሳ መጽሐፍ ቅዱስን ከማንበብ ወደ ኋላ ብለህ ይሆን? ብዙዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ በጣም ከባድ እንደሆነ ይሰማቸዋል። ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ ይበልጥ ደስተኛ እንድትሆንና አርኪ ሕይወት እንድትመራ እንደሚረዳህ ብታውቅስ? እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ አስደሳች እንዲሆንልህ የሚረዱ አንዳንድ ዘዴዎች እንዳሉ ብትረዳስ? መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ አትነሳሳም?

መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ በመጀመራቸው ጥቅም ያገኙ አንዳንድ ሰዎች የተናገሩትን ሐሳብ እስቲ ተመልከት።

በ20ዎቹ ዕድሜ መጀመሪያ ላይ የሚገኘው ኢዚክኤል እንዲህ ብሏል፦ “ቀደም ሲል፣ የት እንደሚሄድ ሳያውቅ ዝም ብሎ መኪና እንደሚነዳ ሰው ነበርኩ። መጽሐፍ ቅዱስን ማንበቤ ግን ሕይወቴ ዓላማ ያለው እንዲሆን ረድቶኛል። በዕለት ተዕለት ሕይወቴ ልሠራበት የምችል ጠቃሚ ምክር ይዟል።”

በ20ዎቹ ዕድሜ ላይ የምትገኝ ፍሪዳ የተባለች ወጣትም እንዲህ ብላለች፦ “ቀደም ሲል ቶሎ እበሳጭ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስን ማንበቤ ግን ራሴን መቆጣጠር እንድችል ረድቶኛል። ይህም በቀላሉ የምቀረብ እንድሆን ስለረዳኝ አሁን ብዙ ጓደኞች ማፍራት ችያለሁ።”

በ50ዎቹ ዕድሜ ላይ የምትገኝ ዩኒስ የተባለች ሴት ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ስትናገር “የተሻልኩ ሰው እንድሆንና መጥፎ ልማዶቼን እንድተው እየረዳኝ ነው” ብላለች።

ከላይ የተጠቀሱትን ጨምሮ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ይበልጥ ደስተኛ ለመሆን እንደሚረዳ ተመልክተዋል። (ኢሳይያስ 48:17, 18) መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ጥሩ ውሳኔዎችን ለማድረግ፣ እውነተኛ ጓደኞችን ለማፍራት፣ ውጥረትን ለመቋቋም፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ ስለ አምላክ እውነቱን ለማወቅ ይረዳል፤ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ከሚያስገኛቸው ጥቅሞች መካከል እነዚህ ጥቂቶቹ ናቸው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው ምክር ምንጭ አምላክ ነው፤ በመሆኑም ምክሩ መቼም ቢሆን የተሳሳተ ሊሆን አይችልም። አምላክ መጥፎ ምክር እንደማይሰጠን የታወቀ ነው።

ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ከማንበብ ወደ ኋላ አትበል። ይሁንና መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ እንድትጀምርና ንባብህን ይበልጥ አስደሳች ለማድረግ የሚረዱ ምን ዘዴዎች አሉ?