የይሖዋ ምሥክሮች ስለ ፍቺ ምን አመለካከት አላቸው?
መጽሐፍ ቅዱስ ጋብቻንና ፍቺን በተመለከተ ያለውን አመለካከት እንከተላለን። አምላክ ጋብቻን የፈጠረው በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል የሚኖር ዘላቂ ጥምረት እንዲሆን አስቦ ነው። ለፍቺ የሚያበቃው ብቸኛው ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክንያት የፆታ ብልግና ነው።—ማቴዎስ 19:5, 6, 9
የይሖዋ ምሥክሮች ትዳራቸው አደጋ ላይ የወደቀ ሰዎችን ይረዳሉ?
አዎ፣ በተለያዩ መንገዶች፦
በጽሑፎች። እነዚህ ጽሑፎች የመቃናት ተስፋ የሌላቸው የሚመስሉ ትዳሮችን ጨምሮ የጋብቻ ጥምረትን ሊያጠናክሩ የሚችሉ ርዕሶችን አዘውትረው ይዘው ይወጣሉ። ለምሳሌ ያህል፣ “የጋብቻ ቃል ኪዳንን አክብሮ መኖር፣” “ይቅር ማለት የምትችሉት እንዴት ነው?” እና “በትዳር ውስጥ የመተማመን ስሜትን እንደገና ማጎልበት” የሚሉትን ርዕሶች ተመልከት።
በስብሰባዎች። በጉባኤ ስብሰባዎቻችንና በትልልቅ ስብሰባዎቻችን ላይ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ትዳር የሚሰጠውን ተግባራዊ ምክር እንማራለን።
በሽማግሌዎች። የጉባኤ ሽማግሌዎች ለባለትዳሮች በግለሰብ ደረጃ እርዳታ ይሰጣሉ፤ እንደ ኤፌሶን 5:22-25 ያሉ ጥቅሶችን ልብ እንዲሉ ይረዷቸዋል።
አንድ የይሖዋ ምሥክር ፍቺ እንዲፈጽም የጉባኤው ሽማግሌዎች ፈቃድ አስፈላጊ ነው?
አይደለም። ሽማግሌዎች በትዳራቸው ውስጥ ችግር የገጠማቸውን ሰዎች እንዲረዱ ሲጠየቁ እንኳ ባለ ትዳሮቹ ምን ማድረግ እንዳለባቸው የመናገር ሥልጣን የላቸውም። (ገላትያ 6:5) ሆኖም፣ ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክንያት ሳይኖረው ፍቺ ለመፈጸም የሚወስን ሰው በጉባኤው ውስጥ ለየት ያሉ መብቶችን ማግኘት አይችልም፤ እንዲሁም ሌላ ሰው ለማግባት ቅዱስ ጽሑፋዊ ነፃነት የለውም።—1 ጢሞቴዎስ 3:1, 5, 12
የይሖዋ ምሥክሮች ስለ መለያየት ምን አመለካከት አላቸው?
መጽሐፍ ቅዱስ ባለትዳሮች አስቸጋሪ ሁኔታዎች ቢያጋጥሟቸውም እንኳ አብረው እንዲቀጥሉ ያበረታታል። (1 ቆሮንቶስ 7:10-16) በትጋት በመጸለይ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎችን ተግባራዊ በማድረግ እንዲሁም ፍቅር በማሳየት ብዙዎቹን ችግሮች መፍታት ይቻላል።—1 ቆሮንቶስ 13:4-8፤ ገላትያ 5:22
ሆኖም አንዳንድ ክርስቲያኖች ቀጥሎ እንደተጠቀሱት ባሉ ከባድ ችግሮች ምክንያት ከትዳር ጓደኛቸው ጋር ለመለያየት ወስነዋል፦
የትዳር ጓደኛቸው መሠረታዊ ነገሮችን ለማሟላት ፈቃደኛ ባለመሆኑ።—1 ጢሞቴዎስ 5:8
የትዳር ጓደኛቸው ከባድ አካላዊ ጥቃት የሚያደርስባቸው በመሆኑ።—መዝሙር 11:5
መንፈሳዊነታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል ሁኔታ በመፈጠሩ። ለምሳሌ ያህል አንድ ባል ወይም ሚስት የይሖዋ ምሥክር የሆነ የትዳር አጋሩ በሆነ መንገድ የአምላክን ትእዛዝ እንዲጥስ ለማስገደድ ይሞክር ይሆናል፤ በዚህ ወቅት ይህ ችግር የደረሰበት የትዳር ጓደኛ ‘ከሰው ይልቅ አምላክን እንደ ገዢው አድርጎ መታዘዝ’ የሚችልበት ብቸኛው መንገድ መለያየት እንደሆነ ይወስን ይሆናል።—የሐዋርያት ሥራ 5:29