በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሽፋኑ ርዕሰ ጉዳይ | ማጽናኛ ማግኘት የምትችለው ከየት ነው?

አምላክ የሚያጽናናን እንዴት ነው?

አምላክ የሚያጽናናን እንዴት ነው?

ሐዋርያው ጳውሎስ ይሖዋን * ‘በሚደርስብን መከራ ሁሉ የሚያጽናናን’ “የመጽናናት ሁሉ አምላክ” በማለት ገልጾታል። (2 ቆሮንቶስ 1:3, 4) በመሆኑም አምላክ ሊሰጠን ከሚችለው እርዳታ በላይ የሆነ ነገር ወይም በሰማይ ያለው አባታችን በሚሰጠን ማጽናኛ ሊወገድ የማይችል ምንም ዓይነት አሳዛኝ ሁኔታ ሊኖር እንደማይችል መጽሐፍ ቅዱስ ማረጋገጫ ይሰጠናል።

እርግጥ ነው፣ አምላክ የሚሰጠውን ማጽናኛ ለማግኘት ከእኛ የሚጠበቅ ነገር አለ። አንድ ሐኪም፣ ለመታየት ቀጠሮ ይዘን ወደ እሱ ካልሄድን እንዴት ሊያክመን ይችላል? ነቢዩ አሞጽ “ሁለት ሰዎች በቀጠሮ ሳይገናኙ አብረው ይጓዛሉ?” በማለት ጠይቋል። (አሞጽ 3:3 የግርጌ ማስታወሻ) በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስ “ወደ አምላክ ቅረቡ፤ እሱም ወደ እናንተ ይቀርባል” በማለት ይመክረናል።—ያዕቆብ 4:8

ታዲያ አምላክ ወደ እኛ እንደሚቀርብ እንዴት እርግጠኞች መሆን እንችላለን? አንደኛ አምላክ እኛን መርዳት እንደሚፈልግ በተደጋጋሚ ተናግሯል። ( ሣጥኑን ተመልከት።) ሁለተኛ፣ በዘመናችንም ሆነ በጥንት ዘመን አምላክ ያጽናናቸው ሰዎች አሉ።

በዛሬው ጊዜ የአምላክን እርዳታ ማግኘት እንደሚፈልጉ በርካታ ሰዎች ሁሉ ንጉሥ ዳዊትም በተደጋጋሚ ከባድ ችግር አጋጥሞታል። በአንድ ወቅት “እርዳታ ለማግኘት ወደ አንተ በምጮኽበት ጊዜ ልመናዬን ስማ” በማለት ይሖዋን ተማጽኖ ነበር። ታዲያ አምላክ መልስ ሰጠው? አዎን። ዳዊት አክሎም “ከእሱ እርዳታ ስላገኘሁ ልቤ ሐሴት ያደርጋል” ብሏል።—መዝሙር 28:2, 7

ኢየሱስ የሚያለቅሱትን በማጽናናት ረገድ የሚጫወተው ሚና

አምላክ፣ ኢየሱስ መጽናኛ በመስጠት ረገድ ቁልፍ ሚና እንዲኖረው አድርጓል። አምላክ ለኢየሱስ ከሰጠው ሥራዎች መካከል ‘ልባቸው የተሰበረውን መጠገን’ እና ‘የሚያለቅሱትን ሁሉ ማጽናናት’ ይገኙበታል። (ኢሳይያስ 61:1, 2) አስቀድሞ በትንቢት እንደተነገረው ኢየሱስ ‘ለደከሙና ሸክም ለከበዳቸው’ ሰዎች ልዩ ትኩረት ሰጥቷል።—ማቴዎስ 11:28-30

ኢየሱስ ለሰዎች ጥበብ ያዘለ ምክር በመስጠት፣ እነሱን በደግነት በመያዝ አልፎ ተርፎም አንዳንዶቹን ከበሽታቸው በመፈወስ አጽናንቷቸዋል። አንድ ቀን የሥጋ ደዌ በሽተኛ የሆነ አንድ ሰው ኢየሱስን “ብትፈልግ እኮ ልታነጻኝ ትችላለህ” በማለት ተማጸነው። ኢየሱስም በርኅራኄ ተገፋፍቶ “እፈልጋለሁ! ንጻ” አለው። (ማርቆስ 1:40, 41) ከዚያም ሰውየው ከበሽታው ተፈወሰ።

በዛሬው ጊዜ የአምላክ ልጅ በምድር ላይ ስለሌለ እኛን በግለሰብ ደረጃ ሊያጽናናን አይችልም። ይሁን እንጂ “የመጽናናት ሁሉ አምላክ” የሆነው አባቱ ይሖዋ መጽናኛ የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ አሁንም እየረዳ ነው። (2 ቆሮንቶስ 1:3) አምላክ ሰዎችን ለማጽናናት የሚጠቀምባቸውን አራት ዋና ዋና መንገዶች እንመልከት።

  • መጽሐፍ ቅዱስ። “በምናሳየው ጽናትና ከቅዱሳን መጻሕፍት በምናገኘው መጽናኛ ተስፋ ይኖረን ዘንድ ቀደም ብሎ የተጻፈው ነገር ሁሉ ለእኛ ትምህርት እንዲሆን ተጽፏል።”—ሮም 15:4

  • የአምላክ ቅዱስ መንፈስ። ኢየሱስ ከሞተ ብዙም ሳይቆይ መላው የክርስቲያን ጉባኤ ሰላም አግኝቶ ነበር። ለምን? “መላው ጉባኤ ይሖዋን በመፍራትና መንፈስ ቅዱስ ከሚሰጠው ማጽናኛ ጋር በመስማማት ይኖር ስለነበር [ነው]።” (የሐዋርያት ሥራ 9:31) የአምላክ ኃይል የሆነው መንፈስ ቅዱስ ከፍተኛ ኃይል አለው። አምላክ በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ የሚገኝን ሰው ለማጽናናት ሊጠቀምበት ይችላል።

  • ጸሎት። መጽሐፍ ቅዱስ “ስለ ምንም ነገር አትጨነቁ” በማለት ይመክረናል። አክሎም እንዲህ ይላል፦ “ከዚህ ይልቅ ስለ ሁሉም ነገር በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር ልመናችሁን ለአምላክ አቅርቡ፤ ከመረዳት ችሎታ ሁሉ በላይ የሆነው የአምላክ ሰላም . . . ልባችሁንና አእምሯችሁን ይጠብቃል።”—ፊልጵስዩስ 4:6, 7

  • የእምነት አጋሮቻችን አስቸጋሪ ሁኔታ ሲያጋጥመን መጽናኛ ለማግኘት በእርግጥ ልንታመንባቸው የምንችል እውነተኛ ጓደኞቻችን ናቸው። ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ እምነት ባልደረቦቹ ሲናገር ‘በችግርና በመከራ’ ወቅት “የብርታት ምንጭ ሆነውልኛል” ብሏል።—ቆላስይስ 4:11፤ 1 ተሰሎንቄ 3:7

ይሁንና ‘እነዚህ ነገሮች፣ ችግር በሚያጋጥመኝ ወቅት በእርግጥ ያጽናኑኛል?’ የሚለው ነገር ያሳስብህ ይሆናል። እስቲ በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ የተጠቀሱ ችግር የደረሰባቸው ሰዎች ያጋጠማቸውን ነገር እንመልከት። እነዚህ ሰዎች “እናት ልጇን እንደምታጽናና፣ እኔም እናንተን ሁልጊዜ አጽናናችኋለሁ” የሚለው አምላክ የሰጠው አስደሳች ተስፋ አሁንም እንደሚፈጸም እርግጠኛ ሆነዋል፤ አንተም ይህንን ማረጋገጥ ትችላለህ።—ኢሳይያስ 66:13

^ አን.3 መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው የአምላክ ስም ይሖዋ ነው።