በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ቃለ ምልልስ | የን ደ ሽዩ

አንድ የፅንስ ጥናት ባለሙያ ስለሚያምንበት ነገር ምን ይላል?

አንድ የፅንስ ጥናት ባለሙያ ስለሚያምንበት ነገር ምን ይላል?

ፕሮፌሰር የን ደ ሽዩ፣ ታይዋን በሚገኘው ብሔራዊ የፒንግቱንግ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የፅንስ ጥናት ዳይሬክተር ነው። በአንድ ወቅት በዝግመተ ለውጥ ያምን ነበር፤ ሳይንቲስት ከሆነ በኋላ ግን አመለካከቱን ቀይሯል። እንዲህ ያደረገበትን ምክንያት ለንቁ! ገልጿል።

እስቲ ስለ አስተዳደግህ በጥቂቱ ንገረን።

የተወለድኩት በ1966 ሲሆን ያደግኩት ደግሞ ታይዋን ውስጥ ነው። ወላጆቼ የታኦይዝምና የቡድሂዝም እምነት ተከታዮች ነበሩ። የቀድሞ አባቶችን እናመልክ እንዲሁም ለምስሎች ጸሎት እናቀርብ የነበረ ቢሆንም ሁሉን ነገር የፈጠረው አምላክ ነው ብለን አስበን አናውቅም።

ባዮሎጂ ለመማር የመረጥከው ለምንድን ነው?

ልጅ ሳለሁ የቤት እንስሳትን መንከባከብ እወድ ነበር፤ በመሆኑም እንስሳትንም ሆነ ሰዎችን ከሚደርስባቸው ሥቃይ እንዴት መገላገል እንደምችል መማር ፈለግኩ። ለተወሰነ ጊዜ የእንስሳት ሕክምና አጠናሁ፤ ከዚያም ስለ ፅንስ (ኤምብሪዮሎጂ) ተማርኩ። ይህ የትምህርት መስክ ሕይወት እንዴት እንደጀመረ ለማወቅ ያስችለኛል ብዬ አስቤ ነበር።

በዚያን ወቅት በዝግመተ ለውጥ ታምን ነበር። ምክንያቱን ልትነግረን ትችላለህ?

በዩኒቨርሲቲ የነበሩት ፕሮፌሰሮች ስለ ዝግመተ ለውጥ ሲያስተምሩ በማስረጃ የተደገፈ ንድፈ ሐሳብ እንደሆነ አድርገው ይናገሩ ነበር። እኔም አመንኳቸው።

መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ እንድትጀምር ያነሳሳህ ምንድን ነው?

ሁለት ምክንያቶች ናቸው። አንደኛ፣ ሰዎች ከሚያመልኳቸው በርካታ አማልክት መካከል አንደኛው ከሁሉ መብለጥ እንዳለበት አስብ ነበር። ይሁንና ‘ይህ አምላክ የትኛው ነው?’ የሚል ጥያቄ ተፈጠረብኝ። ሁለተኛ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ትልቅ ግምት የሚሰጠው መጽሐፍ እንደሆነ አውቃለሁ። በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስን ይበልጥ የማወቅ ፍላጎት አደረብኝ።

በ1992 ቤልጂየም በሚገኘው የሉቨን ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ መማር ስጀምር ወደ አንድ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሄጄ ቄሱን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲያስተምረኝ ጠየቅኩት፤ እሱ ግን ፈቃደኛ አልሆነም።

ታዲያ መንፈሳዊ ጥማትህ የረካው እንዴት ነው?

ከሁለት ዓመት በኋላ፣ በቤልጅየም ሳይንሳዊ ምርምር እያካሄድኩ ሳለ ሩት ከምትባል ፖላንዳዊት ጋር ተዋወቅኩ፤ እሷም የይሖዋ ምሥክር ነበረች። ሩት ስለ አምላክ መማር የሚፈልጉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ለመርዳት ስትል ቻይንኛ ተምራ ነበር። እንዲህ ያለ እርዳታ ለማግኘት ጸልዬ ስለነበረ ከእሷ ጋር በመገናኘቴ ደስ አለኝ።

ሩት፣ መጽሐፍ ቅዱስ የሳይንስ መጽሐፍ ባይሆንም ከሳይንስ ጋር እንደሚስማማ አሳየችኝ። ለምሳሌ የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊ የሆነው ዳዊት እንዲህ ሲል ወደ አምላክ ጸልዮ ነበር፦ “ፅንስ እያለሁ እንኳ ዓይኖችህ አዩኝ፤ የአካሌ ክፍሎች በሙሉ በመጽሐፍህ ተጻፉ፤ አንዳቸውም ወደ ሕልውና ከመምጣታቸው በፊት፣ የተሠሩባቸውን ቀኖች በተመለከተ በዝርዝር ተጻፈ።” (መዝሙር 139:16) ዳዊት ቅኔያዊ አነጋገር የተጠቀመ ቢሆንም በጥቅሉ ሲታይ ጉዳዩን በትክክል ገልጾታል! የአካል ክፍሎች ከመሠራታቸው በፊትም እንኳ እድገታቸው እንዴት እንደሚከናወን የሚገልጽ ዝርዝር መመሪያ ተቀምጧል። መጽሐፍ ቅዱስ ትክክለኛ መሆኑ የአምላክ ቃል ነው ብዬ እንዳምን አስችሎኛል። በተጨማሪም እውነተኛው አምላክ ይሖዋ ብቻ እንደሆነ ተረዳሁ። 1

ሕይወት የተገኘው ከአምላክ ነው ብለህ እንድታምን ያስቻለህ ምንድን ነው?

ሳይንሳዊ ምርምር የሚደረግበት ዓላማ እውነቱ ምን እንደሆነ ማወቅ እንጂ አንድ ዓይነት አመለካከት ይዞ፣ ለዚያ ሐሳብ ድጋፍ ማግኘት አይደለም። ስለ ፅንስ እድገት ያደረግኩት ጥናት አመለካከቴን እንድቀይር ይኸውም ሕይወት በፍጥረት እንደተገኘ እንዳምን አደረገኝ። ነገሩን በምሳሌ ለማስረዳት፣ መሐንዲሶች አንድን ነገር ለመሥራት የሚያገለግሉት ትክክለኛ ዕቃዎች በትክክለኛው ቅደም ተከተልና በተፈለገው ቦታ ላይ እንዲገጣጠሙ የሚያደርጉ መሣሪያዎችን ሠርተው ፋብሪካ ውስጥ ይተክላሉ። የፅንስ እድገት ከዚህ ጋር ሊመሳሰል ይችላል፤ ይሁንና እጅግ ውስብስብ ነው።

ሕይወት የሚጀምረው ከአንድ የዳበረ ሴል ነው መባሉ ትክክል ነው?

አዎ። ከዚያም በአጉሊ መነጽር ብቻ የሚታየው ይህ ሴል ለሁለት ይከፈላል፤ በዚህ መንገድ ሴሎቹ እየተከፋፈሉ ይሄዳሉ። ለተወሰነ ጊዜ የሴሎቹ ብዛት ከ12 እስከ 24 ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ በእጥፍ እየጨመረ ይሄዳል። በዚህ ሂደት መጀመሪያ አካባቢ ስቴም ሴል የሚባሉት ሴሎች ይፈጠራሉ። 2 ስቴም ሴሎች እድገቱን የጨረሰ ሕፃን የሚያስፈልጉትን 200 ገደማ የሚያህሉ የተለያዩ ዓይነት ሴሎች ማስገኘት ይችላሉ። ከእነዚህ መካከል የደም ሴሎች፣ የአጥንት ሴሎች፣ የነርቭ ሴሎችና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

ስለ ፅንስ እድገት ያደረግኩት ጥናት ሕይወት በፍጥረት እንደተገኘ እንዳምን አደረገኝ

ትክክለኛዎቹ ሴሎች በትክክለኛው ቅደም ተከተልና በትክክለኛዎቹ ቦታዎች ላይ መመረት አለባቸው። መጀመሪያ ሴሎች ተሰባስበው ሕብረ ሕዋሳትን ያስገኛሉ፤ እነዚህ ሕብረ ሕዋሳት ደግሞ አንድ ላይ ተሰባስበው የአካል ክፍሎችን ያስገኛሉ። እንዲህ ላለው ሂደት የሚያስፈልገውን መመሪያ ለማዘጋጀት የሚደፍረው የትኛው መሐንዲስ ነው? የሚገርመው ነገር፣ ለፅንስ እድገት የሚያስፈልገው መመሪያ በዲ ኤን ኤ ውስጥ ተጽፎ ይገኛል። ይህ ሁሉ ነገር ምን ያህል ውብ እንደሆነ ሳስብ ንድፍ አውጪው አምላክ ነው ብዬ እንዳምን ያደርገኛል።

የይሖዋ ምሥክር እንድትሆን ያደረገህ ምንድን ነው?

በአጭሩ ፍቅር ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ “እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ ሰዎች ሁሉ ደቀ መዛሙርቴ እንደሆናችሁ በዚህ ያውቃሉ” ብሏል። (ዮሐንስ 13:35) ይህ ከአድልዎ ነፃ የሆነ ፍቅር ነው። የሰዎች ዜግነት፣ ባሕል ወይም የቆዳ ቀለም በዚህ ረገድ የሚያመጣው ለውጥ የለም። ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መሰብሰብ ስጀምር እንዲህ ያለውን ፍቅር መመልከትም ሆነ ማጣጣም ችያለሁ።

^ 2. ፕሮፌሰር የን ደ ሽዩ በክርስቲያናዊ ሕሊናው የተነሳ የሰው ልጆችን ፅንስ ስቴም ሴል መጠቀም የሚጠይቅ ሥራ አይሠራም።