በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሥላሴ ልታምንበት የሚገባ ትምህርት ነው?

ሥላሴ ልታምንበት የሚገባ ትምህርት ነው?

ክርስቲያን ነን የሚሉ ከሁለት ቢሊዮን የሚበልጡ ሰዎች አሉ። አብዛኞቹ አብያተ ክርስቲያናት የሥላሴን መሠረተ ትምህርት ማለትም አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ ናቸው የሚለውን ትምህርት ያስተምራሉ። ሥላሴ፣ በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ ተቀባይነት ያለው መሠረተ ትምህርት ሊሆን የቻለው እንዴት ነው? ደግሞስ ይህ መሠረተ ትምህርት መጽሐፍ ቅዱስ ከሚያስተምረው ነገር ጋር ይስማማል?

መጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ ያለቀው በአንደኛው መቶ ዘመን ዓ.ም. ነው። ለሥላሴ መሠረተ ትምህርት መነሻ የሆነው ትምህርት መዳበር የጀመረው ደግሞ በ325 ዓ.ም. ይኸውም መጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ ካለቀ ከሁለት መቶ ዓመት የሚበልጥ ጊዜ ካለፈ በኋላ ነው፤ በዚህ ወቅት በትንሿ እስያ በምትገኝ ኒቂያ የተባለች ከተማ (በአሁኗ ኢዝኒክ፣ ቱርክ) ጉባኤ ተካሂዶ ነበር። ኒው ካቶሊክ ኢንሳይክሎፒዲያ እንደሚገልጸው የኒቂያ ጉባኤ እንዳወጣው በሚነገረው ድንጋጌ ላይ የአምላክንና የክርስቶስን ማንነት ጨምሮ ቤተ ክርስቲያን ስለምታስተምራቸው ትምህርቶች ለመጀመሪያ ጊዜ መግለጫ ተሰጠ። ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ ካለቀ በመቶ ከሚቆጠሩ ዓመታት በኋላ ስለ አምላክና ስለ ክርስቶስ ማንነት መግለጫ መስጠት ያስፈለገው ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እነዚህ አስፈላጊ የሆኑ ርዕሰ ጉዳዮች የያዘው ሐሳብ ግልጽ ስላልሆነ ነው?

ኢየሱስ ሁሉን ቻይ አምላክ ነው?

ቆስጠንጢኖስ የሮምን ግዛት ብቻውን ማስተዳደር በጀመረበት ወቅት፣ ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች በአምላክና በክርስቶስ መካከል ስላለው ዝምድና የተለያየ አመለካከት ነበራቸው። ኢየሱስ፣ ሁሉን ቻይ አምላክ ነው? ወይስ ፍጡር ነው? ቆስጠንጢኖስ ለዚህ ውዝግብ እልባት ለመስጠት ሲል የአብያተ ክርስቲያናት መሪዎችን ወደ ኒቂያ ጠራ፤ በእርግጥ ይህን ያደረገው እውነቱን ማወቅ ፈልጎ ሳይሆን ግዛቱ በሃይማኖት ምክንያት እንዲከፋፈልበት ስላልፈለገ ነው።

“ለእኛስ . . . አንድ አምላክ አብ አለን።”—1 ቆሮንቶስ 8:6 የ1954 ትርጉም

ቆስጠንጢኖስ፣ በመቶዎች ይቆጠሩ የነበሩትን ጳጳሳት አንድ ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ጠየቃቸው፤ ያሰበው ግን ሊሳካለት አልቻለም። በመሆኑም ቆስጠንጢኖስ፣ ኢየሱስ ከአብ ጋር “በባሕርዩ አንድ” (ኦሞዩስዮስ) እንደሆነ የሚገልጸውን አሻሚ ሐሳብ ጉባኤው እንዲያጸድቅ ሐሳብ አቀረበ። ቅዱስ ጽሑፋዊ ያልሆነውና በግሪክ ፍልስፍና ላይ የተመሠረተው ይህ ቃል ከጊዜ በኋላ በአብያተ ክርስቲያናት እምነት ውስጥ ለተካተተው የሥላሴ ትምህርት መሠረት ሆኗል። ሥላሴ ዛሬ ያለውን መልክ የያዘው በአራተኛው መቶ ዘመን መገባደጃ ላይ ሲሆን መንፈስ ቅዱስም የሥላሴ ክፍል እንደሆኑ ከሚነገርላቸው አማልክት አንዱ እንደሆነ የተገለጸው በዚህ ወቅት ነው።

ይህ ጉዳይ ሊያሳስብህ የሚገባው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ “እውነተኛ አምላኪዎች አብን . . . በእውነት” እንደሚያመልኩ ተናግሯል። (ዮሐንስ 4:23) ይህ እውነት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይገኛል። (ዮሐንስ 17:17) ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ አንድም ሦስትም እንደሆኑ ያስተምራል?

በመጀመሪያ ደረጃ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ሥላሴ” የሚለው ቃል አይገኝም። በሁለተኛ ደረጃ ኢየሱስ፣ ሁሉን ቻይ ከሆነው አምላክ ጋር እኩል እንደሆነ ፈጽሞ ተናግሮ አያውቅም። ይልቁንም ኢየሱስ ሁሉን ቻይ የሆነውን አምላክ አምልኳል። (ሉቃስ 22:41-44) ሦስተኛ ደግሞ ኢየሱስ ከተከታዮቹ ጋር የነበረውን ዝምድና እንመልከት። ኢየሱስ መንፈሳዊ አካል ሆኖ ከሞት ከተነሳ በኋላም ተከታዮቹን “ወንድሞቼ” ብሎ ጠርቷቸዋል። (ማቴዎስ 28:10) ታዲያ የኢየሱስ ተከታዮች፣ ሁሉን የሚችለው አምላክ ወንድሞች ነበሩ ማለት ነው? እንዳልነበሩ ጥያቄ የለውም። ከዚህ ይልቅ የአምላክ የበኩር ልጅ በሆነው በክርስቶስ በማመናቸው እነሱም አንድ የሆነው አባት ልጆች መሆን ችለዋል። (ገላትያ 3:26) እስቲ የኒቂያ ጉባኤ ድንጋጌ እንደሆነ የሚገለጸውን ሐሳብ ቀጥሎ ከቀረቡት ጥቅሶች ጋር አወዳድር።

የኒቂያ ድንጋጌ ምን ይላል?

“በእግዚአብሔር ልጅ በአንድ በኢየሱስ ክርስቶስም እናምናለን፣ . . . ከአባቱ ባህርይ፣ ከእውነተኛ አምላክ የተወለደ እውነተኛ አምላክ፣ የተወለደ እንጅ ያልተፈጠረ፣ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን።”—የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

  • “ከእኔ [ከኢየሱስ] አብ ይበልጣል።”—ዮሐንስ 14:28 *

  • “እኔ [ኢየሱስ] ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁም ዐርጋለሁ።”—ዮሐንስ 20:17

  • “ለእኛስ . . . አንድ አምላክ አብ አለን።”—1 ቆሮንቶስ 8:6

  • “የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ።”—1 ጴጥሮስ 1:3

  • “አሜን የሆነው [ኢየሱስ]፣ . . . በእግዚአብሔርም ፍጥረት መጀመሪያ የነበረው እንዲህ ይላል።”—ራእይ 3:14 *

^ አን.13 ጥቅሶቹ የተወሰዱት ከ1954 ትርጉም ነው።

^ አን.17 ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለው መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት የሚረዳ መጽሐፍ “አምላክን በተመለከተ ትክክለኛው ትምህርት የቱ ነው?” እና “ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው?” የሚሉ ሁለት ምዕራፎች አሉት። ይህን መጽሐፍ ከይሖዋ ምሥክሮች ማግኘት ወይም www.ps8318.com/am በተባለው ድረ ገጽ ላይ ማንበብ ትችላለህ።